Wednesday, May 23, 2012

ቅዱስ ሲኖዶስ በተሐድሶ ኑፋቄ አራማጅ ድርጅቶች ላይ የቀረበውን ጥናታዊ መግለጫ እና የውሳኔ ሐሳብ አጸደቀ፤ ማ/ቅዱሳንም ከሰ/ት/ቤቶች መምሪያ ሥር እንዲወጣና ራሱን እንዲችል ወሰነ

የቅዱስ ሲኖዶስ ዐሥርኛ ቀን የቀትር በፊት ውሎ

  • በፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ አራማጅ ግለሰቦች ላይ የቀረበውን ጥናታዊ መግለጫና የውሳኔ ሐሳብ ደግሞ ከሰዓት በኋላ በመነጋገር እንደሚያጸድቀው ይጠበቃል:: 
  • ማኅበረ ቅዱሳን በአወቃቀሩ ከሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሥር ወጥቶ ለዋና ሥራ አስኪያጁ ተጠሪ እንዲኾን ቅዱስ ሲኖዶሱ ወስኗል
 የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በዛሬው ዐሥርኛ ቀን የቀትር በፊት ውሎው በስምንት የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ እንቅስቃሴ አራማጅ ድርጅቶች ላይ የብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት እና የሊቃውንት ጉባኤ አባላት ጥምር ኮሚቴ ያቀረበውን ጥናታዊ መግለጫ እና የውሳኔ ሐሳብ መርምሮ አጽድቋል፡፡

Friday, May 18, 2012

በብዙ ጫና ውስጥ ያለው ማ/ቅዱሳን መንግሥት በዋልድባ አካባቢ ስለሚገነባቸው ፕሮጄክቶች ሪፖርቱን አቀረበ

 ማ/ቅዱሳን መንግሥት በዋልድባ አካባቢው ሊሠራው ስላቀደው ግዙፍ ፕሮጄክት “አጠናሁት” ያለውን ሪፖርት አቀረበ፤ ከመንግሥት ጋር መነጋገሩንም ገለጸ። ዛሬ ይፋ የተደገው የማኅበሩ ሪፖርት የቤተ ክህነቱ አዳዲስ ተሿሚዎች ማኅበሩን በዋልድባ ጉዳይ በከሰሱ ማግስት የቀረበ ሲሆን ለእነርሱ ክስ የተሰጠ አፋጣኝ ምላሽ ይሁን አይሁን ወደፊት የሚታይ ይሆናል።
አዲስ የተሾሙት የሰንበት ት/ቤቶች ማ/መምሪያ ኃላፊ መምህር ዕንቁ ባሕርይ ተከስተ “በዋልድባ አካባቢ መንግሥት ሊሠራ ያቀደውን ግዙፍ የስኳር ፋብሪካን በማስመልከት በዋልድባ ይዞታ ላይ ያደረሰው ተጽእኖ መኖር አለመኖሩን የሚያጣራ ኮሚቴ ተቋቁሞ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ሁሉ ተፈላጊውን የማጣራት ሥራ አከናውኖ” ከተመለሰ በኋላ “ጋዜጣዊ መግለጫ መሰጠቱና … የማኅበረ ቅዱሳን ጋዜጠኞች መከታተላቸው መሣተፋቸውና የሚፈልጉትን ጥያቄ በይፋ አቅርበው ምላሽ መሰጠቱ”ን ጠቅሰው “ማንኛውም ጋዜጠኛ በተለይም ደግሞ የቤተ ክርስቲያኒቱ ልሣን የሆነው የማኅበሩ ጋዜጣና መጽሔት መረጃ ከወሰደ በኋላ መግለጫውን አለማውጣቱ አግባብነት የሌለው ከመሆኑም በላይ የሚዲያ ሥነ ምግባርንም ያልተከተለ ስለሆነ” ጽሑፉ ያልወጣበትን ምክንያት ማኅበሩ በጽሑፍ ይገልጽ ዘንድ ከሕዝብ ግንኙነት መምሪያ መታዘዛቸውን እንዳብራሩ መዘገባችን ይታወሳል።

የመምሪያው ደብዳቤ “ጋዜጣዊ መግለጫውን በሚዲያ ለማውጣት ተስማምታችሁ ሪፖርት እንድታደርጉ ከወሰናችሁ በኋላ ዘገባው የቀረበት ምክንያት በጽሑፍ ለማደራጃ መምሪያው” እንዲመለስ እንደሚጠብቅ በመግለጽ “ለፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር፣ ለብሔራዊ ደኅንነት አገልግሎትና ለፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን” ግልባጭ ተደርጓል። ደጀ ሰላምም “የቅ/ሲኖዶስ ጽ/ቤት፣ የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽ/ቤት፣ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት፣ የሕዝብ ግንኙነት መምሪያ እና ሕግ አገልግሎት መምሪያ የቤተ ክርስቲያናችን አካላት ስለሆነ በቀጥታም ባይሆን ጉዳዩ ሊያገባቸው ይችላል። ከላይ ስማቸው የተዘረዘሩት የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች በምን አግባብ ነው ስለ አንድ ማኅበር፣ ያውም በአንድ መምሪያ ሥር ስላለ አካል ግልባጭ የሚደረግላቸው? መንግስታዊ መሥሪያ ቤቶቹ ከሚዲያ ጋር የተገናኙ እንኳን ቢሆኑ በግድምድሞሽ “ግንኙነት አላቸው” ይባል ይሆናል። ፌዴራል ጉዳዮች፣ ደኅንነት፣ ፖሊስ … መጠቀሳቸው ለምን ያስፈልጋል? እሰሩልን፣ ግደሉልን፣ ቀፍዱድልን ለማለት ካልሆነ” ማለቷ ይታወሳል።

ቅ/ ሲኖዶስ በፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ አራማጅ ማኅበራትና ግለሰቦች ላይ የተዘጋጀውን ሪፖርት አዳመጠ

  • ኮሚቴው ፍጹም ውግዘት የሚገባቸውን የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ እንቅስቃሴ አራማጅ ማኅበራትና ግለሰቦች ለይቷል - ማኅበረ ሰላማ፣ ማኅበረ በኵር፣ የምሥራች አገልግሎት፣ አንቀጸ ብርሃን፣ የቅድስት ልደታ ለማርያም መንፈሳዊ ማኅበር፣ የኢትዮጵያ መንፈሳዊ ተሐድሶ ኅብረት፣ አሸናፊ መኰንን፣ አግዛቸው ተፈራ፣ ጽጌ ስጦታው እና ግርማ በቀለ ይገኙባቸዋል።
  • “ሃይማኖቴ እንደ አባቶቼ ነው” ያሉት የአባ ሰረቀ እና “የቅን ልቦና የመንፈሳዊና የፈውስ አገልግሎትን ያቋቋምኹት ልጆቼን የማበላቸው ስለተቸገርኹ ነው” ያሉት የ‹ሊቀ ካህናት› ጌታቸው ዶኒ ጉዳይ ያለውሳኔ ሐሳብ ለምልአተ ጉባኤው ውሳኔ ቀርቧል።
  • አባ ጳውሎስ ከጥንተ አብሶ ጋራ በተያያዘ ስለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ንጽሕና እንዲመሰክሩ ሊጠየቁ ይችላሉ።
  • ሊቃውንት ጉባኤው ተደጋጋሚ ጥሪ አድርጎለት ያልቀረበው በጋሻው ደሳለኝ ዛሬ ጠዋት የሊቃውንት ጉባኤውን ሰብሳቢ በእጅጋየሁ በየነ አማላጅነት ሲለማመጥ ታይቷል፤ ሊቃውንት ጉባኤው “በአንድ ወቅት በራስ ቅል ኮረብታ ላይ ኢየሱስና ዲያቢሎስ ቁማር ተጫወቱ . . . ዲያቢሎስም በጨበጣ ገባ” የሚለውና ሌሎቹም ጥንቃቄ የጎደላቸው ንግግሮቹ ፍጹም ውግዘት የሚገባቸው እንደኾኑ አመልክቷል።
  • የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን አመራርና መዋቅር ይሻሻላል፤ በጠቅላላ ጉባኤና በቦርድ ይመራል፤ የኮሚሽኑ ሊቀ ጳጳስ የኮሚሽኑ ኮሚሽነር እንደሚኾኑ ተጠቁሟል።
  • የማኅበራት መመሪያ ረቂቅ ለውይይት ቀርቧል፤ አሁን ባሉበት አኳኋን ከቀጠሉ “ሌላ ሲኖዶስ ይኾናሉ፤ የፖሊቲካ ዓላማ ማስፈጸሚያ ይኾናሉ፤ በቀኝ ዘመምና ግራ ዘመም አቋም ቤተ ክርስቲያኒቷን ይውጣሉ/ይከፍላሉ” የሚል ስጋት የቀረበባቸው ማኅበራት ንብረት በአጥቢያ አብያተ ክርስቲያን መዋቅር ውስጥ ተጠቃልሎ እንዲተዳደር ሐሳብ ቀርቧል፤ የመመሪያውን ረቂቅ በጥንቃቄ የተመለከቱት የምልአተ ጉባኤው አባላት ጉዳዩ በይደር እንዲታይ አድርገዋል።

 የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በግንቦት 8 ቀን 2004 ዓ.ም ስድስተኛ ቀን ውሎው በፕሮቴስታንት ድርጅቶች ከፍተኛ ድጋፍ እየተደረገላቸው የቤተ ክርስቲያናችንን ትምህርተ ሃይማኖት ለማፋለስ፣ ሥርዐተ እምነቷን ለመለወጥ፣ አገልጋዩንና ምእመኑን ለመከፋፈል በቡድንና በድርጅት ኾነው በመንቀሳቀስ ላይ ስለሚገኙት የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ አራማጅ ማኅበራትና ግለሰቦች የተዘጋጀውን ሪፖርት አዳምጧል፡፡

ቅዱስ ሲኖዶሱ በአጀንዳ ተ.ቁ (13) ላይ ስለ ሃይማኖት ሕጸጽ በተመለከተው ርእሰ ጉዳይ በጥቅምቱ ቅዱስ ሲኖዶስ መደበኛ ስብሰባ ከሊቃውንት ጉባኤ ጋራ በመኾን የቀረቡ ማስረጃዎችን መርምረው የውሳኔ ሐሳብ የሚያቀርቡ ሰባት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በአባልነት የሚገኙበት ኮሚቴ ሠይሞ ነበር፡፡

በወቅቱ የኮሚቴው አባላት እንዲኾኑ ተመርጠው የነበሩት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፡- ብፁዕ አቡነ ናትናኤል፣ ብፁዕ አቡነ ገሪማ፣ ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ፣ ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ፣ ብፁዕ አቡነ እንድርያስና ብፁዕ አቡነ ያሬድ ነበሩ፡፡ ጥቅምት 20 ቀን 2004 ዓ.ም ከተሠየመው ከእኒህ የኮሚቴው አባላት መካከል ሦስቱ (አቡነ ናትናኤል፣ አቡነ ቄርሎስ እና አቡነ እንድርያስ) በተለያየ ምክንያት መቀጠል ስላልቻሉ ቋሚ ሲኖዶሱ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስን፣ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስንና ብፁዕ አቡነ ኤጲፋንዮስን ተክቷል፡፡

ኮሚቴው ከሊቃውንት ጉባኤው የቀረበለትና መርምሮ በትናንትናው ዕለት ከቀትር በኋላ በጸሐፊው በኩል ለቅዱስ ሲኖዶስ በንባብ ያሰማው ሪፖርት ባለ60 ገጽ ሲኾን በዛሬው ዕለት ምልአተ ጉባኤው በሪፖርቱ ላይ በመወያየት የውሳኔ ሐሳቡን ያጸድቃል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ሪፖርቱ በፕሮቴስንታንት ድርጅቶች ከፍተኛ ድጋፍ እየተደረገላቸው ኦርቶዶክሳውያን መስለው በሁሉም የቤተ ክርስቲያን እንቅስቃሴዎች በመሳተፍ እና የአስተዳደር መዋቅሮች ውስጥ በመሰግሰግ ፕሮቴስታንታዊ አጀንዳቸውን ለማስፈጸም ከሚንቀሳቀሱት ማኅበራት መካከል በስምንቱ ላይ ያተኮሩ የኅትመት ውጤቶችን፣ የድምፅ እና ምስል ማስረጃዎችን መርምሯል፡፡

የፕሮቴስታንት እምነት ተቋማት ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጋራ ያላቸውን የመሠረተ እምነት /ዶግማ/ ልዩነት /ድንበር/ አጥፍተው ቤተ ክርስቲያናችንን በቁጥጥር ሥር አውለው ባለችበት ፕሮቴስታንታዊ ማድረግ ወይም ቤተ ክርስቲያናችንን  የጦርነት ቀጣና በማድረግ እንደ ሕንድ ቤተ ክርስቲያን ለሁለት መክፈል ዓላማ ያላቸው ማኅበራቱ በአሁኑ ሰዓት በሚያወጧቸው መጻሕፍትና መጽሔቶች እንዲሁም በራሪ ወረቀቶች የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ በግልጽ ይቃወማሉ፤ አገልጋዩና ምእመኑ በማይመች አካሄድ እንዲጠመድ እና በዘረኝነት እንዲከፋፈል ጭምር ይንቀሳቀሳሉ፡፡ ይህም በማስረጃ ተደግፎ የቀረበ በመኾኑ ፍጹም መወገዝ ያለባቸው ማኅበራት ተለይተው ቀርበዋል፡፡

ከእኒህም ውስጥ ኮሚቴው ፍጹም ውግዘት እንዲተላለፍባቸው የውሳኔ ሐሳብ ከቀረበባቸው የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ አራማጅ ማኅበራት መካከል፡-
1.   ማኅበረ ሰላማ - በክልል ትግራይ ፍትሕ ቢሮ ተመዝግቦ ፈቃድ ባወጣበት ስሙ ማኅበረ ሰላማ ምትሕግጋዝ ማኅበር (Abune Selama Self Help Association) እየተባለ የሚጠራና ዋና ጽ/ቤቱ መቐለ የሚገኝ ነው፡፡ ባወጣው ፈቃድ መሠረት በልማት ሥራ ላይ መሳተፍ ሲገባው ከሕገ ወጥ ባሕታውያንና ሌሎች የተሐድሶ ማኅበራት ጋራ በመቀናጀት ‹‹በገዳማት ላይ ጥናት ማድረግ›› በሚል ሰበብ በቅርሶች ላይ ከፍተኛ ዘመቻ በማካሄድ ማንነትን ለማጥፋትና በአቋራጭ ለመክበር ይንቀሳቀሳል፤ ዘረኝነትን ያስፋፋል፡፡ የአሲራ መቲራው ገዳም አበምኔት ነኝ ባዩ አባ ገብረ መድኅን ገብረ ጊዮርጊስ ከማኅበሩ መሪዎች ጋራ በድብቅ በመገናኘት ዕቅዱን ለማስፈጸም ይንቀሳቀሳል፡፡
2.   ማኅበረ በኵር - በ1983 ዓ.ም የተመሠረተ ሲኾን መሥራቹ በ1953 ዓ.ም ከቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የተባረረው መሠረት ስብሐት ለአብ ነው፡፡ ከምሥረታው ጀምሮ ሙሉ በሙሉ በፕሮቴስታንቶች ድጋፍ ላይ የተመሠረተ ነው፡፡ ሌሎች የተሐድሶ ኑፋቄ ማኅበራት ‹‹አርኣያችን ነው›› ይሉታል፡፡ ጮራየተሰኘ መጽሔት ያሳትማል፡፡ መጽሔቱን በሕገ ወጥ መንገድ ለብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ለሰንበት ት/ቤቶችና ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ግቢ ግባኤያት ይልካሉ፡፡ በአሁኑ ወቅት  አግዛቸው ተፈራ የተባለው በዋና አዘጋጅነት በሚሠራበት መጽሔት የጸሎት መጻሕፍትን ይቃወማሉ፤ አባቶችን ይዘልፋሉ፤ አዋልድ መጻሕፍትን አይቀበሉም፤ ‹‹ቅዱሳት ሥዕላት አያስፈልጉም›› ይላሉ፤ ‹‹ኢየሱስ ክርስቶስ አሁንም አማላጅ ነው››፤ ሥልጣነ ክህነትን አይቀበሉም፤ የእምነት ልዩነት ድንበርን ያፈርሳሉ፤ ‹‹ቅዱስ ቍርባን መታሰቢያ ነው፤ ውላጤ ኅብስት የለም›› ይላሉ፤ ምስጢረ ሜሮንን ይቃወማሉ፤ ‹‹ሥጋ በተዋሕዶ የባሕርይ አምላክ አልኾነም›› ይላሉ፡፡
3.   የምሥራች አገልግሎት - በ1990 ዓ.ም የተመሠረተና አሸናፊ ሲሳይ በተባለ ግለሰብ የሚመራ ሲኾን ‹‹ቤተ ክርስቲያን የውጊያ ቀጣና ናት›› በማለት ለእንቅስቃሴው የሚረዱ 34,000 ‹‹እርሾዎችን›› በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ለመሰግሰግ ከፍተኛ የገንዘብና የማቴሪያል ድጋፍ የሚደረግለት፣ እያንዳንዳቸው ከ100 - 160 አባላት ባሉት ኅቡእ ቡድን (Cell based) የሚንቀሳቀስ አካል ነው፡፡ ‹‹ፕሮቴስታንት እና ኦርቶዶክሳውያን በመሠረተ እምነት አንድ ናቸው›› ከሣቴ ብርሃን ከተባለው ድርጅት ጋራ አንድ ዐይነት ዓላማ ያራምዳል፤ የክርስቶስን አምላክነት በአግባቡ አያምንም፤ ምንኵስናን ይቃወማል፤ አዋልድ መጻሕፍትን አይቀበልም፡፡
4.   አንቀጸ ብርሃን - ከሰበታ መካነ ሰላም ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ፍሬ ሃይማኖት ሰንበት ት/ቤት ተለይቶ የወጣው አሸናፊ መኰንን የሚያሳትማቸውን የኑፋቄ መጻሕፍት ያስተዋውቃል፡፡ በሌላ ስያሜው ራሱን ‹‹ማኅበረ መንፈስ ቅዱስ›› እያለ ይጠራል፡፡ ‹‹የኢ////ያን እምነትና ሥርዐት የጠበቀ መንፈሳዊ ጽሑፍ›› በሚል በኅቡእ በሚያሰራጫቸው ጽሑፎቹ ምሥጢረ ሥላሴን አፋልሶ ያስተምራል፤ ምስጢረ ሥጋዌን በማፋለስ ቅብዐትን ይሰብካል፤ በካህን ፊት የሚደረግ ኑዛዜን ይቃወማል፡፡
5.   የቅድስት ልደታ ለማርያም መንፈሳዊ ማኅበር - በኑፋቄያቸው ከማኅደረ ስብሐት ልደታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን ተክለ ሳዊሮስ ሰንበት ት/ቤት የተሰናበቱ ተወግዞ የተባረረው የሃይማኖተ አበው ማኅበር ሰለባዎች ነው፡፡ አቶ መስፍን በተባለ ግለሰብ ይመራል፡፡ ኦርቶዶክሳውያን ወደ ፕሮቴስታንትነት መቀየራቸውን ሳያውቁት ሃይማኖታቸውን የሚያስክዱ የርቀት ትምህርቶችን ይሰጣል፤ ኅትመቶችን ያሰራጫል፤ ቤተ ክርስቲያንን በግልጽ ይዘልፋል፤ የሥጋ ወደሙን አማናዊነት አያምንም፡፡
6.   የእውነት ቃል አገልግሎት - ድርጅቱ ይህን ስያሜ ከመያዙ በፊት በመጀመሪያ BGNLJ (Brothers Gathered Unto Lord Jesus) በኋላም (Bible Truth Ministry) እየተባለ ይጠራ ነበር፡፡ በአሁኑ ጊዜ የድርጅቱ መሪ በቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ ደቀ መዛሙርትና ማኅበረሰብ ብርታት የተባረረው ግርማ በቀለ ነው፡፡ ሌላው ተጠቃሽ ግለሰብ ሥዩም ያሚ የሚባለው ነው፡፡ ድርጅቱ ከእንግሊዝኛ በሚተረጉማቸው መጻሕፍት የቤተ ክርስቲያንን መጻሕፍት ክፉኛ ያብጠለጥላል፤ በየክልሉ በከፈታቸው ቅርንጫፍ ማከፋፈያዎች ጽሑፎችን በነጻ በማደል፣ ሥልጠናዎችን በመስጠት፣ ታሪክን በማዛባትና በአዋልድ መጻሕፍት ላይ የማይገባ ትችት በመሰንዘር አገልጋዮችን ያደናግራል፡፡

Thursday, May 17, 2012

ማ/ቅዱሳን መንግሥት በዋልድባ አካባቢ ስለሚገነባው የስኳር ፕሮጄክት “መልካምነት” ባለመዘገቡ ተጠየቀ፤ መልስ እንዲሰጥ ይጠበቃል


አስከትሎም “ስለሆነም ማንኛውም ጋዜጠኛ በተለይም ደግሞ የቤተ ክርስቲያኒቱ ልሣን የሆነው የማኅበሩ ጋዜጣና መጽሔት መረጃ ከወሰደ በኋላ መግለጫውን አለማውጣቱ አግባብነት የሌለው ከመሆኑም በላይ የሚዲያ ሥነ ምግባርንም ያልተከተለ ስለሆነ” ጽሑፉ ያልወጣበትን ምክንያት ማኅበሩ በጽሑፍ ይገልጽ ዘንድ ከሕዝብ ግንኙነት መምሪያ መታዘዙን ያብራራል።

የመምሪያው ደብዳቤ አክሎም “ጋዜጣዊ መግለጫውን በሚዲያ ለማውጣት ተስማምታችሁ ሪፖርት እንድታደርጉ ከወሰናችሁ በኋላ ዘገባው የቀረበት ምክንያት በጽሑፍ ለማደራጃ መምሪያው” እንዲመለስ እንደሚጠብቅ ይገልጻል። ደብዳቤው በአድራሻ ለማኅበሩ ከተላከ በኋላ ደግሞ ለቤተ ክህነቱ የተለያዩ አካላትና በመንግሥትም በኩል “ለፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር፣ ለብሔራዊ ደኅንነት አገልግሎትና ለፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን” ግልባጭ ተደርጓል።

የቅ/ሲኖዶስ ጽ/ቤት፣ የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽ/ቤት. የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት፣ የሕዝብ ግንኙነት መምሪያ እና ሕግ አገልግሎት መምሪያ የቤተ ክርስቲያናችን አካላት ስለሆነ በቀጥታም ባይሆን ጉዳዩ ሊያገባቸው ይችላል። ከላይ ስማቸው የተዘረዘሩት የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች በምን አግባብ ነው ስለ አንድ ማኅበር፣ ያውም በአንድ መምሪያ ሥር ስላለ አካል ግልባጭ የሚደረግላቸው? መንግስታዊ መሥሪያ ቤቶቹ ከሚዲያ ጋር የተገናኙ እንኳን ቢሆኑ በግድምድሞሽ “ግንኙነት አላቸው” ይባል ይሆናል። ፌዴራል ጉዳዮች፣ ደኅንነት፣ ፖሊስ … መጠቀሳቸው ለምን ያስፈልጋል? እሰሩልን፣ ግደሉልን፣ ቀፍዱድልን ለማለት ካልሆነ።

Monday, May 14, 2012

አቡነ ጳውሎስ ከፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ መናፍቃን ጋራ ማበራቸውን የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ገለጹ

 (ምንጭ ደጀ ሰላም፤ ግንቦት 5/2004 ዓ.ም፤ May 13/ 2012)፦



  • ቅዱስ ሲኖዶስ በቀጣይ ለሚኖረው አመራር የመላው ካህናትና ምእመናን ጸሎትና ሁለንተናዊ ድጋፍ እንዲደረግለት ተጠይቋል 
  • በአባ ጳውሎስ፣ አባ ፋኑኤልና ኀይለ ጊዮርጊስ ጥላሁን ምክርና ኮሚሽን አድራጊነት የተጻፈው የዜና ቤተ ክርስቲያን ጋዜጣ ርእሰ አንቀጽ እና ዘገባ በፈጠረው ቁጣ ሳቢያ የቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባ ተቋረጠ 
  • ጋዜጣው በስብሰባ መካከል መሰራጨቱና ባተኮረበት ይዘት ብፁዓን አባቶችን ለማሸማቀቅ ተብሎ መዘጋጀቱን የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ተናግረዋል 
  • የጋዜጣው ርእሰ አንቀጽና ዘገባዎች አባ ጳውሎስ በስብሰባው እንዲያዙላቸው የሚፈልጓቸውን አጀንዳዎች ከአባ ጳውሎስ “የፓትርያርክነት ዐምባገነንነት” ፍላጎት አንጻር የማብራራት ግብዝነት የሚታይበት ነው
  • አባ ጳውሎስን ከፓትርያርክነት ማዕርጋቸው በሚያወርዷቸው የቃለ መሐላ ጥሰትና የታማኝነት መታጣት ጉዳዮች ዙሪያ ጠንካራ ውይይት ተጀምሯል
  • የአባ ጳውሎስ ግብረ በላዎች ትንት ማምሻውንና ዛሬ ቀን በአባቶች ማረፊያ ቤት እየተዘዋወሩ በማስፈራራት ጽናታቸውንና አንድነታቸውን ለማላላት እየሞከሩ ነው፤ እጅጋየሁ በየነ፣ ኀይለ ጊዮርጊስ ጥላሁንና ለጊዜው ስማቸው ያልተጠቀሱ ግለሰቦች ይገኙባቸዋል
  • መደበኛ ስብሰባው ነገ ሰኞ ይቀጥላል
  ግንቦት 4 ቀን 2004 ዓ.ም ከቀትር በፊት በነበረው የቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባ ርእሰ መንበሩ አባ ጳውሎስ በምልአተ ጉባኤው ስምምነት የተደረሰባቸውን አጀንዳዎች ባለመቀበል ኾነ ብለው በያዙት ግትርነት የተነሣ ብዙኀኑ አባላት ከቀትር በኋላ ሌላ ሰብሳቢ መርጠው ውይይታቸውን ለመቀጠል ወስነው ነበር የተነሡት፡፡
በዚህ መሠረት የቅዱስ ሲኖዶሱ አባላት ከቀትር በኋላ ስብሰባውን ለመቀጠል ወደ አዳራሹ ሲገቡ የዜና ቤተ ክርስቲያን ጋዜጣ በየመቀመጫቸው አንጻር ተቀምጦ ያገኛሉ፤ ፓትርያርኩም በኮሚቴው የተዘጋጁትን አጀንዳዎች እንደሚቀበሉ መስለው ተላስልሰው በመቅረባቸው ምልአተ ጉባኤው በእርሳቸው ርእሰ መንበርነት እየተመራ በተ.ቁ (2) ላይ የተመለከተውን የቅዱስ ሲኖዶሱን ዋና ጸሐፊ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤልን ሪፖርት አዳመጠ፤ እግረ መንገዳቸውንም ጋዜጣውን እንደ ዋዛ መመልከታቸውን አላቆሙም ነበር፡፡
ሪፖርቱ በንባብ ተሰምቶ ከተጠናቀቀ በኋላ ውይይት ከመጀመሩ በፊት ለሻሂ ዕረፍት የተነሡት አባቶች ግን ጋዜጣው በያዘው ‹ቁም ነገር› ላይ መመካከር ያዙ፤ ምክክሩም አቡነ ጳውሎስ ከስብሰባው ቀደም ብለው ከዋሽንግተን ወደ አገር ቤት ከመጡት አባ ፋኑኤል እና ኀይለ ጊዮርጊስ ጥላሁን ጋራ በማበር የጋዜጣውን አዘጋጆች እና ጋዜጣው በሚዘጋጅበት መምሪያ ውስጥ በሓላፊነት የሚገኙ ሌሎች ግለሰቦችን በቅጥረኝነት በመጠቀም የሠሩት መኾኑን ይደርሱበታል፡፡
ከሻሂ ዕረፍት መልስ ጋዜጣው ምን እንደጻፈ፣ ስለምን እንደጻፈ ሊያውቅና ሲቆጣጠርም ይገባ የነበረው  የስብከተ ወንጌል እና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ ስለ ጋዜጣው ዝግጅት ምንም እንደማያውቁና ሌሎች አጀንዳዎች ወደ ኋላ ቀርተው ምልአተ ጉባኤው በዚሁ ጉዳይ እንዲነጋገር ይጠይቃሉ፡፡ ከዚህ በኋላ በቤቱ የነበረው ድባብ በፓትርያርኩ እና በአባ ፋኑኤል ላይ ባነጣጠረ የተግሣጽ መአት የተሞላ ነበር፡፡ አባ ጳውሎስም ይኹኑ አባ ፋኑኤል የሠሩትን ያውቃሉና አንገታቸውን አቀርቅረው ተግሣጻቸውን ከመቀበል ውጭ ትንፍሽ ያሉት ነገር አልነበረም፡፡
በተግሣጹ አባ ጳውሎስ ከተሐድሶ መናፍቃን ጋራ በግልጽ በማበር አባቶች በወቅታዊ ጉዳዮች በተቀረጹት አጀንዳዎች ዙሪያ ያላቸውን አንድነት እና የዓላማ ጽናት በመሸርሸር ለማሸማቀቅ (በግብር የሚመስሏቸው የመፍቀሬ ፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ብሎጎች እንደሚያደርጉት) አስበው እንዲፈጸም በማዘዝ እጃቸው እንዳለበት ተነግሯቸዋል፤ አባ ፋኑኤልም “መወገዝ ያለብኽ ሕገ ወጡ አንተ ነኽ፤ በሌላው ሊቀ ጳጳስ ሀገረ ስብከት ገብተኽ ክህነት የምትሰጥ፤ አንተ ብሎ ክህነት ያዥ¡” በሚሉና ሌሎችም ኀይለ ቃላት የድርሻቸውን አግኝተዋል፡፡
በ56ኛ ዓመት ቁጥር 126፣ ሚያዝያ ግንቦት 2004 ዓ.ም ታትሞ በወጣው ዜና ቤተ ክርስቲያን ጋዜጣ ላይ ‹‹የአባቶች ገበና በሕገ ቤተ ክርስቲያን ሲጋለጥ›› በሚል ርእስ ስለ ሰፈረው ርእሰ አንቀጽ፣ ‹‹ቤተ ክርስቲያንንና መንጋዎቿን ከወቅታዊ አደጋ ለመታደግ ከግንቦቱ ቅዱስ ሲኖዶስ የሚጠበቅ የህልውና ውሳኔ›› በሚል ርእስ ስለተዘጋጀው ሐተታ አስተያየታቸውን የተጠየቁት ዋና አዘጋጁ መጋቤ ምስጢር ወልደ ሩፋኤል ፈታሒ ‹‹እኔ ማንንም አልፈራም፤ ጽሑፉ አያስጠይቀኝም እንጂ ብጠየቅበት አልፈራም፤ በይዘቱ አዲስ አይደለም፤ የተለያዩ ግለሰቦች በየራሳቸው አቀራረብ ሲጽፉት የቆዩት ነው፤ እኔ ለመጻፍ የሞከርኹት የቤተ ክርስቲያን ህልውና እየተነካ ነው ብዬ በማምንበት ስለ ጳጳሳት ንብረት ጉዳይ ነበር፤ አባ ጳውሎስ ግን በሲኖዶስ ስብሰባ ሕገ ቤተ ክርስቲያን ይሻሻል አሉ፤ እውነቱን ለመናገር  ጽሑፉ ከውጭ የመጣ እንጂ በዝግጅት ክፍሉ የተጻፈ አይደለም፤ በስሜ እየተነገደብኝ ነው፤›› ብለዋል፡፡
ዋና አዘጋጁ ጽሑፉ ከውጭ ተዘጋጅቶ እንደመጣ የተናገሩትን መነሻ በማድረግ አዘጋጁን አካል ለማወቅ በተደረገ ጥረት÷ ‹‹አባ ጳውሎስን ደግፋችኹ ከጻፋችኹ ማንም አይነካችኹ፤ ከተነካችኹም እኛ አለንላችኹ፤ ሁሉም ወንጀለኛ ነው›› በሚል የጥቅም ማበረታቻ የተቀበሉት የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ሕዝብ ግንኙነት መምሪያ ዋና ሓላፊ እስክንድር ገብረ ክርስቶስ፣ በስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ ዋና ሓላፊነት ባለው ሥልጣን ቀናዒ ኦርቶዶክሳውያንን ከመድረክ እያገለለና በየአህጉረ ስብከቱ በመዞር ከፕሮቴንታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ አራማጆችና አቀንቃኞች ጋራ ያለውን ግንኙነት እያጠናከረ የሚገኘው አእመረ አሸብር፣ እንደ ቀበሮዋ ዘለው ዘለው የሻቱትን ማዕርገ ጵጵስና ቢያጡት የተሾሙትን አባቶች በማሸማቀቅና አንገት በማስደፋት ለመሾም የቋመጡት አባ ሰረቀ፤ ለዚህም የገንዘብ ድጋፍ የሰጡት አባ ፋኑኤልና ዦቢራው ኀይለ ጊዮርጊስ ጥላሁን መኾናቸው እየተነገረ ነው፤ የአባ ጳውሎስ አይዟችኹ ባይነት (ቡራኬ) ሳይዘነጋ ማለት ነው፡፡ ይኹንና የዝግጅት ክፍሉም በጽሑፉ ላይ ማሻሻያ በማድረግና እንዲታተም በመፍቀድ፣ ምናልባትም የጥቅሙም ተካፋይ በመኾን መጠየቁ እንደማይቀር ግልጽ ነው፡፡