Tuesday, March 26, 2013

“ሰማዕታት የዚችን ዓለም ጣዕም ናቁ”  ዓለም እንደየዘመኑ የተለያየ ጠባይ አላት፤ ልክ እንደ እስስት ትለዋወጣለች፡፡ ስለዚህ ሁል ጊዜ ከእውነት ይልቅ ሐሰት፥ ከፍቅር ይልቅ በእውነተኞቹ ላይ ጥላቻ፥ በግልጽ ይታይባታል፡፡ የራሷ የሆነውን እጅግ አድርጋ ትወዳለች ስለዚህም በተለያየ መረብ እያጠመደች ለዘለዓለሙ ትጥላለች፡፡ “ሰማዕታት” /ምስክሮች/ ግን የዚችን ዓለም ጣዕም ናቁ፤ ማለትም እውነት እግዚአብሔርን፥በሐሰት ጣዖት አልለወጡም ስለዚህ በእግዚአብሔር ዘንድ በክብር ተቀምጠው ስለ እኛ እያማለዱ አሉ፡፡

አለማመኔን እርዳው

በመ/ር ኃይለማርያም ላቀው
«እምነት፣ ተስፋ ስለምናደርገው ነገር የሚያስረዳ ነው» ዕብ. 11፣1፡፡ የሰው ልጅ ተስፈኛ ወይም ተስፋ ያለው ፍጡር ነው፡፡ አዳም ቢበድልም እንኳን ቸሩ አምላክ በኋላ ዘመን ከልጅ ልጁ ተወልዶ እንደሚያድነው ተስፋ ሰጥቶታል፡፡ አዳምም የመዳኑን ነገር በእምነት ተስፋ በማድረጉ በጊዜው አግኝቶታል፡፡ እምነት ለእግዚአብሔር ያለንን ፍቅር የምንገልጥበት፣ እርሱን ደስ የምናሰኝበት የሕይወት መሠረት ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እምነት እግዚአብሔርን ደስ የምናሰኝበት ጥበብ መሆኑን ሲያስረዳ «ያለ እምነት እግዚአብሔርን ደስ ማሰኘት አይ ቻልም» ብሏል፡፡ ዕብ. 11፣6፡፡ 

በዘመነ ብሉይ የነበሩ በእምነት ጥን ካሬአቸው የተመሰከረላቸው አበውና እመው በእግዚአብሔር በመታመናቸው በሚያቃጥል የእሳት ነበልባል ውስጥ በመጣል፣ ወደ አንበሳ ጉድጓድ በመወርወር፣ በሰይፍ በመተርተር እምነታቸውን ገልጠዋል፡፡ እግዚአብሔርም በቅዱሳን የእምነት ጥንካሬ የልበ ደንዳኖችን ልብ ማርኳል፡፡ «ንጉሡ ናቡከደነጾር ለጣዖት አንሰግድም ብለው እምነታቸውን የገለጡትን ሠለስቱ ደቂቅን ርዝማኔው አስራ ስድስት ክንድ ከሚደርስ የእሳት ነበልባል ውስጥ በሰንሰለት አስሮ ቢወርወራቸውም ከሰውነታቸው አንዳች ሳይቃጠል በመዳናቸው፤ «በእርሱ የታመኑትን ባሪያዎቹን ያዳነ የሲድራቅ፣ የሚሳቅና የአብ ደናጎ አምላክ ይባረክ» ዳን. 3፣25 ሲል የሠለስቱ ደቂቅን አምላክ አክብሯል፡፡