Monday, July 2, 2012

ለምን አልሰለምሁም? ክፍል ሦስት የቅዱሳት መጻሕፍት ታማኝነት፤


ያለፉት ሁለት ክፍሎች ምስጢር ሥላሴና ምስጢረ ሥጋዌ የተረጋገጡት በቅዱሳት መጻሕፍት ነው፡፡ የቅዱሳት መጻሕፍትን ታማኝነት ለማስተባበል እነዲዳት ሞክረዋል፤ ቁርአን ግን ያረጋግጣል፡፡ሁሉንም እናስከትላለን፡፡ (2ጢም.3 ፡16-17) ቅዱስ መጽሐፍ በሙሉ በእግዚአብሔር መንፈስ መሪነት የተጻፈ ነው፤ እርሱ እውነትን ለማስተማር፤ የተሳሳቱትን ለመገሠጽ፤ ስሕተትን ለማረምና ለትክክለኛ ኑሮ የሚበጀው መምሪያ ለመስጠት ይጠቅማል፡፡ የሚጠቅመውም የእግዚአብሔር ሰው ፍጽም እንዲሆንና ማንኛውንም መልካም ሥራ ለመሥራት ብቁ እንዲሆን ነው፡፡
በዚህ መሠረት የቅዱሳት መጻሕፍት ደራስያን ሁለት ሁለት ናቸው፤ አንድኛው የሃይማኖትን ሂደት የሚመራው መንፈስ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ፣ ሁለተኛው የእያንዳንዱ መጽሐፍ አዘጋጅ ራሱ ደራሲው፡፡ ለሁለቱም ድርሻ ድርሻ አላቸው፤ መንፈስ ቅዱስ በስውር በደራሲው መንፈስ አድሮ ይመራል፤ ደራሲው ደግሞ ብራና ፍቆ፣ ዳምጦ፣ ቀለም በጥብጦ፣ የሚጽፍበትን ቋንቋ አጥንቶ፣ በተቻለ ዐቅም ተዘጋጅቶ ይቀርባል ፡፡ እንደዚህ ያለውን በፍጽም አእምሮው ያለውን ሰው መንፈስ እግዚአብሔር ይመራዋል እንጂ ዕፅ ፈርስ ጠጥቶ እንደ አበደ፡አብዶም እንደሚለፈልፍ አያስቀባጥረውም፤ወይም አብሾ ጠጥቶ እንደ ሰከረ አያስቀባጥረውም፤ ያለዚያም ዛር እንደ ያዘው አያስጎራውም፡፡

ስለዚህ ቅዱስ መጽሐፍ በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ስለተጻፈው በይዘቱ አይጠላም፣ አይፋለስም፣ አይጋጭም፣ ግን ደራሲው ሰው በመሆኑ በእርሱ ድርሻ፣ የቃላት ግድፈት ፣ የአገባብ (የአሰካክ) የጾታ የግሥ ጊዜ ስሕተት ይገኙበታል፤ ሩቅና ቅርብ፣ አይጠብቅም፣ ሴትና ወንድ (ጾታ)አይለይም፡፡ በትርጉምም የዘሩን ቋንቋ ስልት ወደ ሚገለበጥበት ቃል ለቃል ይመልስና፣ ብዙ ጊዜ በተቀባዩ ቋንቋ ግጭት ያጋጥመዋ፡፡ ከዚህ በቀር እነአሕመድ ዲዳት እንደሚሉት ግጭት የለም፤ እንደ ቁርአንም አይፋለስም፡፡ እንደ ቁርአን የያዘውን ርእስ ሳይጨርስ፣ ርእስ መከተል እንዳልተማረ ከአምስተኛ ክፍል በታች እንዳለ ሕፃን ተማሪም በአንድ ርእስ ዐሥራ አምስት ሐሳብ አይናገርም፡፡ የያዘውን ሒሳብ ሳይጨርስም ሌላ ሐሳብ ትዝ አለኝ ብሎ አይዘላብድም፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ተሰብስቦ ከተጠረዘ እንኳንስ በአመራርና በይዘት ይቅርና በአንድ ቀለም ወይም ቃል እንኳ ቢሆን ብዙ ያናግራል፣ ሲያናግር ሲያጨቃጭቅ ኑሮአል፡፡ ይታረማል ቢባልስ መጽሐፍ ቅዱሳን ያህል የእግዚአብሔር ቃል፣ ከእግዚአብሔር ጋራ የተነጋገሩ ነቢያት፣ ሐዋርያት፣ የተማሩ ሊቃውንት የጻፉት፣ ራሱ ወልደ አምላክ ያስተማረው፣ እንዴት ጤና በሌለው፣ ባልተማረ፣ ፊደል ባልቆጠረ ሰው በእየጊዜው በተለፈለፈ፣ ከእሱ በፊት የነበረ አዋልድና የባልቴት ተረት ተይዞ አንድ አዲስ ነገር ያልተያዘ ዝብርቅርቅ እርስ በእርሱ የሚፋለስ መጽሐፍ ይዞ ይነቅፋል? ከዚህ ላይ ደርግ በመጣ ጊዜ የደረሰ አንድ ቀልድ መሳይ ታሪክ ትዝ ይለኛል፡፡ ሁለት የለውጥ ሐዋርያት ፍኖተ ሰላም ሂደው ስለለውጡ የመሰላቸውን ካወሩ በኋላ፣ለተሰብሳቢው የጥያቄ መብት ይፈቅዳሉ፣ ከተሰብሳቢዎች አንዱ እጁን ያወጣና ጌታው! ለምን ነው? ጃንይሆን ያወረዳችኋቸው? ብሎ ይጠይቃል፣ የለውጥ ሐዋርያም ሌባ ስለሆኑ ነው ብሎ ይመልሳል፤ ጠያቂም ታዲያ አንድ ሌባ በመቶ ሃያ (120) ነው ወይ የሚለውጥ? ብሎ ቁጭ አለ፡፡ ይዘቱ፣ አመራሩ ፣ ሂደቱ የተዝረጠረጠ መጽሐፍ ይዞ ፣ሆሄና ቀለም መጽሐፍ ቅዱስ ጎደለው ብሎ ይወቅሳል፡፡ ለምን ቢሉ የራሱን ጉድለት ሰው እንዳያይበት፡፡
ምሳሌያት፤
ሀ. አላህ አንድ ነው ይላል፤ ራሱ በነጠላም በብዙም ይናገራል፤ (ሱራህ፡4164,) ከዚህ በፊት ያነሣልህን ያላነሣንልህም ካለ በኋላ፣ አላህ በቀጥታ ለሙሴ ተናገረ ብሏል፡፡ እኛና ነጠላ አላህ በአንድ ዐረፍተ ነገር አይሄድም፡፡
ለ. (ሱራ፡5፡14) ስለዚህ በመካከላቸው ጠላትነትና ጠብ አላህ የእጃቸውን ሥራ እስከ ሚነግራቸው እስከ ትንሣኤ ድረስ አንሥተናል፡፡ አሁንም ነጠላና ብዙ፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍት ግን ልክ እንደሆኑ ራሱ ቁርአን ከ40 ጊዜ በላይ እየመሰክረ ጽፎአል፤ ለምሳሌ፤
1. (ሱራህ. 5፡46) በውስጧ  መመሪያና ብርሃን ያለበት ኦሪትን አወረድን፤ ትእዛዝን የተቀበሉት ነቢያትም በአይሁድ ላይ በእርሷ ይፈርዳሉ።……። በነቢያት ፈለግም ላይ ለማርያም ልጅ ኢየሱስ ኦርትን የምታረጋግጥ ወንጌልን ሰጠነው። እርሷም በውስጧ ቀትታና ብርሃን አለባት።…የወንጌል ባለቤቶችም እግዚአብሔር ባወረደው በወንጌል ይፍረዱ።።እግዚአብሔር  ባወረደው፡፡ የማይፈርድ ዐመፀኛ ነው፡፡ (ራሱ መሐመድም)
2. ወደ ቀኝ እንድትመሩ ለሙሴ የጽድቅንና የኀጢአትን መስፈርት መጽሐፍ ሰጠን፡፡ (ሱራህ 2፡53 87፤)
3.  በእርግጥ ለሙሴ መጽሐፍ ሰጥተን በኋላውም አእላፍ ልኩካን (ነቢያት) እንዲከተሉት አደረግን፡፡ ለማርያም ልጅ ኢየሱስም የአምላክ ሥልጣን እንዳለው ግልጥ መረጃ ሰጥተን በመንፈስ ቅዱስ አጠናነው፡፡ ከዚህም በላይ የቅዱሳትን መጻሕፍት ታማኝነትና እውነተናነት የሚከተሉት የቁርአን ጥቅሶች ያረጋግጣሉ፡፡ (ሱራህ፡ 121፤144፤174፤176፤213፤285፤ ሱራህ 111፡7፤ 20፤23፤48፤78፤81፤100፤ ሱራህ 4፡ 46፤51፤105፤ሱራህ 6፡155፤ ሱራህ 119፡47፤
ከዚህም በላይ ይህን ያህል መጥቀስ ይቻላል፡፡ ይህ ሁሉ ምስክር እያለ ነው እነዲዳት መጽሐፍ ቅዱስ ተቆነፃጽሏል የሚሉት፣ ከኪሳቸው አውጥተው፡፡ ምክንያቱም አመዛዝኖ መረዳት አነጻጽሮ ማንበብ አያውቁምና ነው፡፡

2 comments:

  1. ቃለ ህይወት ያሰማልን ደስ የሚል ነው ይቀጥል

    ReplyDelete
  2. ቃለ ህይወት ያሰማልን

    ReplyDelete