Friday, June 29, 2012

ለምን አልሰለምሁም? ክፍል ሁለት ምሥጢረ ሥጋዌ


ስለ ምሥጢረ ሥጋዌ በሰፊው ለክርስቲያን በብዙ ቦታዎች ተጽፎል፡፡ 
ለነዲዳትና ለመሰሎቹ በመልስና በመረጃ መልክ ስለ ምሥጢረ ሥጋዌ በአጭሩ ተገልጧል፡፡ 

እሱም በመጀመሪያ የኦሪትን ከዚያ የቁርአንን ስለአዳም መውደቅ ታሪክ መነሻ አድርጎ ታትቷል፡፡
(ዘፍ 2፡7) ከዚህ በኋላ እግዚአብሔር አምላክ ከመሬት አፈር ወስዶ፣ ሰውን ከአፈር አበጀው፣ በአፍንጫውም የሕይወት እስትንፋስ እፍ አለበት፡፡ ሰውም ሕይወት ያለው ፍጡር ሆነ፡፡
(ዘፍ 2፡15)ከዚህ በኋላ እግዚአብሔር አምላክ ሰውን በኤደን የአትክልት ቦታ አኖረው፤ይህንም ያደረገው ሰው የአትክልቱን ቦታ እንዲያለማውና እንዲኩተኩተው ነው፤ እግዚአብሔር አምላክ ሰውን በአትክልቱ ቦታ ከሚገኙት ዛፎች ሁሉ ፍሬ ብላ፤ ነገር ግን ደጉን ከክፉ ለመለየት የሚያስችል ዕውቀት ከሚሰጠው ዛፍ ፍሬ አትብ፤ ምክንያቱም ከዚህ ፍሬ በበላህበት ቀን በርግጥ ትሞታለህ ብሎ አዘዘው፡፡
(ዘፍ 2፡18) እግዚአብሔር አምላክም አለ፤ ሰው ብቻውን ይሆን ዘንድ መልካም አይደለም፡፡ የሚመቸውን ረዳት እንፍጠርለት፡፡
(ዘፍ 2፡20) ----- ፤ እግዚአብሔር አምላክም በአዳም ከባድ እንቅለፍን ጣለበት አንቀላፋም፣ ከጎድኑም አንዲት አጥንት ወስዶ ስፍራውን በሥጋ ሞላው፤ እግዚአብሔር አምላክም ከአዳም የወሰዳትን አጥንት ሴት አድርጎ ሠራት፤ ወደ አዳምም አመጣት፣ አዳምም ይህች አጥንት ካጥንቴ፣ ሥጋም ከሥጋዬ ናት እርስዋ ከወንድ ተገኝታለችና ሴት ትባል፡፡ ስለዚህ ሰው አባትና እናቱን ይተዋል፣ ከምሽቱም ይጣበቃል፤ ሁሉም አንድ ሥጋ ይሆናሉ፡፡ አዳምና ምሽቱ ሁለቱም ዕራቁታቸውን ነበሩ፡፡ አይተፋፈሩምም ነበር፡፡
(ዘፍ.3፡1……፣)አዳምና ሔዋንም በዚህ ሁኔታ በገነት መካከል የፍጥረታት ሁሉ ገዥዎች ሁነው ሲኖሩ ሰይጣን ቀናና በእባብ ተመስሎ የተከለከለችውን ዕፅ እንዲበሉ በማድረጉ የአምላካቸውን ትእዛዝ በመተላለፋቸው ተረግመው ከገነት ወጡ፡፡ 
ይህ ታሪክ በቁርአን ደግሞ እንዲህ ነው፤ (ላሟ ምዕራፍ ፡2፡34-38) መላእክትንም ለአዳም ስገዱ ባልነ ጊዜ ከዲያብሎስ በቀር ሁሉም ስገዱ፣ እሱ ግን እምቢ አለ፣ ኮራም በዚህም ከከሐዲዎች ተቆጠረ አዳም ሆይ !አንተ ከነምሽትህ በገነት ተቀመጥ፤ ከርሷም በፈለጋችሁት ስፍራ በሰፊው ተመገቡ፣ ግን ይህችን ዛፍ አትቅረቡ፤ ከበደለኞች ትሆናላችሁና አልነም፡፡ ከርሷም ሰይጣን አዳልጦ (አሳስቶ) በውስጡ ከነበሩበት ድሎት አወጣቸው፡፡ አንዱ ለሌላው ጠላት ሁናችሁ ውረዱ፣ ለእናተም በምድር ላይ እስከ ጊዜያችሁ ድረስ መጠለያና ሥንቅ አለላችሁ፡፡ በኦሪትም ሆነ በቁርአን እግዚአብሔር ትእዛዙ በመጣሱ አዝኖ አዳምና ሔዋንን ከገነት እንዳስወጣቸው ቁልጭ ተደርጎ ተጽፏል፡፡ ቁርአን ከዚህ በኋላ ስለመታረቅና ድኅነት የሚናገረው የለም፣ ከአሕዛብ ልማድ ከመጣው መሥዋዕተ እንስሳ በቀር፡፡ ኦሪትና ወንጌል ግን በትንቢትና በፍጻሜ አምላክ ዓለምን የታረቀው በልጁ ደም መሆኑን አብራርተው፣ ነግረው ደምድመዋል እዳም የፈጣሪውን ትእዛዝ በመተላለፍ ከገነት ወጥቶ፣ እሱ ብቻ ሳይሆን በመላ ዘሩም በምድረ ፋይድ ሲኖር በሦስት አካላት ሲመሰገን የሚኖር እግዚአብሔር በዳዩን አዳምን ይቅር ለማለት ወሰነ፡፡(ዘፍ.3፡1-4) ለዚህም መታረቂያ መሥዋዕት አስፈለገ፡፡ በደሉም ግዙፍ ስለሆነ ለመሥዋዕቱ የሰውና የእንሰሳ ደም የማይበቃ ሆነ፡፡ የስላሙ የመሐመዱ፣ የቁርአኑ አምላክ ቢሆን ኑሮ ያፍርድ እንደ ዐጤ ስለሚሰራ ምሬሃለሁ ቢል ይበቃ ነበር፡፡ የአብርሃም አምላክ ግን እውነተኛ ዳኛም መሓሪም ስለሆነ፣ ተቀዳሚና ተከታይ የሌለው ልጁ ሥጋ ለብሶ እንዲሠዋ ወሰነና ላከው፡፡ (ዘፍ.3፡15) በአንተና በሴቲቱ መካከል፣ በዘርህና በዘርዋ መካከል  ጠላትነትን አኖራለሁ፤ እርሱ ራስህን ይቀጠቅጣል አንተም ሰኮናውን ትቀጠቅጣለህ ባለው መሠረት፣ በዳይም ተበዳይም ልጅ ልጃቸውን አዋጡና የአምላክ ልጅ እግዚአብሔር ወልድ፣ ኢየሱስ ክርስቶስ ፣ሥጋ ለብሶ፣ ትስብአርትን ተዋሕዶ የሰውን ልጅ ጠላት ሰይጣንን ድል ነሥቶ ፣ ከዲያብሎስ ባርነት ከሲኦልና ከገሃነም ሥቃይና ኩነኔ አዳነ፡፡ የተበዳይና የበዳይ ልጅ (ዘር) በተዋሕዶ ሥጋ ተሰቅሎ ዓለምን አዳነ፡፡ ከሦስቱ ሥላሴ፣ ከሠለስቱ አካላት አንዱ በተለየ አካሉ እግዚአብሔር ወልድ ሥጋ ለብሶ፣ ተሠቃይቶ፣ ተገፎ፣ ተገርፎ፣ ተሰቅሎ ዓለምን እንዲያድንና ከአባቱም ከራሱም ከመንፈስ ቅዱስም ጋራ እንደያስታርቅ እንዴት እንደ ተወሰነ በሥሉስነት ሲመሰገን ከሚኖረው ከገናናውና ከረቂቁ አምላክ አንዱ እግዚአብሔር በቀር ማንም አያውቅ፡፡ ተበዳዩ አምላክ በዳዩን ሰውን ይቅር የሚልበት ጊዜ ሲደርስ፣ በመበሠሩ በቅዱስ ገብርኤል አማካይነት፣ የቅድስት ድንግል ማርያምን ይሁን ይደረግልኝ ፈቃድ ብኋላ፣ አንድያ፣ ተቀዳሚ፣ ተከታይ የሌለው ልጁን ሥጋ እንዲዋሃድ እንዲለብስ ወደ ቅድስት ድንግል ማርያም ላከ፡፡

በልደት ሦስቱም፤ አብ፣ ወልድ፣ መንፈስ ቅዱስ ተስማምተዋል፣ ተባብረዋል፡፡ አብ መርጧል፣አጽንቷል፤ መንፈስ ቅዱስ በላያዋ ላይ አድሮ ወላዲተ አምላክ ማኅደረ መለኮት እንድትሆን አመቻችቷል፣ አዘጋጅቷታል፡፡ እግዚአብሔር ወልድም ከነፍሷ ነፍስ ከሥጋዋ ሥጋ ነሥቶ ፍጹም ሰው ሁኗል፡፡ ስለዚህም በአንድ አካል የተዋሐደ ሰውና አምላክ ይባላል፡፡ ስለዚህም በአንድ እረኛ አንድ መንጋ በተሰጠው ውሳኔ አንድ መለትስ ይባላል፤ (መለትስም ሰውና አምላክ ወይም መለኮትና  ትሰብእት ማለት ነው) በመለኮቱ የአብ ልጅ፣ በትስብእቱ (ሥጋው) የማርያም ልጅ ይሉሃል ይህ ነው፡፡ በግዕዙም ወልደ አብ በመለኮቱ ወልደ ማርያም በትስብእቱ ይላል ውሳኔው፡፡ ሰው አምላክ፣ አምላክ ሰው ሆነ የሚያሰኘውም ይህ ነው፡፡ በመለኮቱ አምላክ አማልክት፣ ፈጣሬ ዓለማት ሲሆን፣ በትስብእቱ ደግሞ ንጉሠ ነገሥት፣ ሊቀ ካህናት፣ ሊቀ ሰማዕት፣ ሊቀ ነቢያት ነው፡፡ እንደ ሰውነቱ፣ ሰው መሆኑን ለማጠየቅ ትንሽ በትንሽ አድጓል፣ እንደ ሕፃናት አልቅሷል፣ደክሟል፣ ተርቧል፣ ተጠምቷል፣ ምራቅ፣ ደም ወጥቶታል፣ ሙቷል፡፡ አምላክ እንደ መሆኑ፣ አምክነቱን ለማጠየቅ (ለማስረዳት) በድንግልና ተወልዷል፣ በተዘጋ ቤት ገብቷል፣ በባሕር ላይ ያለ ጀልባ ሂዷል፤ ከሞተና ከተቀበረ በኋላ መቃብር ክፈቱልኝ መግነዝ ፍቱልኝ ሳይል ተነሥቷል፤ በዚህም አንደ መለትስነቱን እነረዳለን፡፡መለትስ መሆኑን ያልተረዱ ብዙ ሰዎች ትስብእትን ሲያይ የተነገሩትን ቃላት፣ ጥቅሶች፣ ዐረፍተ ነገሮች፣ ባነበቡ ቁጥር ለማረም ወይንም ለማጣመም ይሞክራሉ፡፡ ይህ ግን ካለማወቅ የመጣ ነው፤ ልኩ መለኮቱነ ሲያዩ የተነገሩትን ለመለኮቱ ሰጥቶ በመለኮት ባሕርይ መተርጎም፣ በትስብእት፣ ለትስብእት የተነገሩትን ደግሞ ለትስብእት ሰጥቶ ከነበቡ በኋላ አንድ  አካል አንድ መለትስ ብሎ አስታርቆ አስማምቶ መፍታት ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ እግዚአብሔር ወልድ የአብና የማርያም ልጅ፣ በአንድ መለትስ መሆኑን ለመረዳት በሰፊው የሚፈልግ ሁሉ ወደ ፊት በሌሎች ክፍሎች የምናየው ይሆናል፡፡ ከዚህ ግን ፍጽም አምላክ እና ፍጹም ሰው በአንድ አካል እንድመለትስ መሆኑን ለማስረዳት የሚከተሉት ተጠቅሰዋል፤ (ዮሐ.1፡1-14) 3፡1618፤ መዝ.2፡68፤ 109፡4፤ ሉቃ.23፡34፤ ዮሐ.10፡30፤14፡6፤20፡17፤ ኢሳ.61፡13፤ ሉቃ.418-19፤53፡11-12፤ ዮሐ.14፡28፤31፤ መዝ. 21፡1፤ ማቴ.27፡46፤ ሉቃ.13፡32፤ 2ቆሮ.1፡3፤11፡31፤ ኤፌ.1 ኢሳ.3፤17፤ ፊል.2፡6፣10፤ 1ጴጥ.1፡3፤ 2ጴጥ 1፡17-18፤ ግብ.ሐዋ 2፡24፤ ራእ.1፡6፤3፡12 ዮሐ.6፡37-39፤7፡29፤ 1፡36፤8፡42፤9፡4፤ ሉቃ.4፡43፤ ገላ.4፡4፤ ዮሐ.4፡9) ከቅዱሳት መጻሕፍት አምላክና ሰው መሆኑን ለመግለጥ የተጻፈ ለቁጥር የሚዳግቱ ብዙ ጥቅሶች አሉ፡፡ቁርአንም የእግዚአብሔር ቃል መሆኑን ያምናል፤ ይህንም

Monday, June 25, 2012

ለምን አልሰለምሁም? ክፍል አንድ ምስጢረ ሥላሴ


ኢየሱስ ክርስቶስ ምስጢረ ሥላሴን አላስተማረም፣ የአምላክ ልጅም አይደለም፣ አምላክ ልጅ ነኝም አላለም እያሉ ዓለምን ለሚያወናብዱት ለነአሕመድ ዲዳት ማብራሪያ  

ከጥንት ጀምሮ እግዚአብሔር በአካል አንድ ብቻ አልነበረም፡፡ በአካል በስም፣ በግብር ሦስት፣ በመለኮት፣ በባሕርይ በህልውና አንድ ሁኖ አንድ አምላክ እየተባለ ዘለዓለም ሲቀደስ ኑሯል፤ይኖራል፡፡
ሥላሴ በስም:- አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ይባላሉ፡፡ በግብር አብ ይወልዳል፤ ያሠርጻል፤ ወልድ፤  ይወለዳል፤ መንፈስ ቅዱስ ይሠርጻል፡፡ በአካል አብም፤ ፍጹም አካል (ህልውና፤ ገጽ) አለው፤ እንደዚሁም ወልድና መንፈስ ቅዱስ ከአብ የተለየ ፍፁም አካላት አሏቸው። አካልና ሰውነትን  ያልተማሩ ሰዎች ያደባልቋቸዋል፤ አካል ሦስቱም፣አብ ወልድ ፡ መንፈስ ቅዱስ ለእየራሳቸው አሏቸው ሰውነት ግን የሚጨበጥ የሚዳሰስ ያለው ወልድ ብቻ ነው፡፡ ይኽውም ሥጋ በመልበሱ፡፡ በምስጢረ ሥላሴ አካል ለቀዋሚ ነገር ለመንፈስ ነው የሚነገረው፤ አይታይም አይዳሰስም፤ መንፈስ ነው፡፡ አካል በምናውቃቸው በሌሎቹ ቋንቋዎች (ፕሮሶፓን ግሪክ፤ ፔርሶና ላቲን፤ ፔርሶን እንግሊዝ፣ ጣልያን ፈረንሳይ ነው፡፡ ሰውነት (በአልካ በሚዳሰስ ትርጉሙ)ሶማ ግሪክ፣ ቦዲእንገሊዘ፡ ኮርም ጣልያን፡ በፈረንሳይ በንባብ ኮር በአፃፃፍ ኮርጥስ፡ ላቲን ኮርፑስ ነው፡፡ ስለዚህ ነው ወልድ ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ በተለየ ረቂቅ አካሉ ሥጋ ስለለበሰ። ሰውነት(የሚዳሰስ አካል) አለው የሚባለው፡፡ ባሕሪያቸው መለኮታቸው፣ መንግሥታቸው፣ ሥልጣናቸው ግን አንድ ነው፡፡ በአካል ሦስት ስለሆኑና በመለኮት፣ በባሕርይ አንድ ስለሆኑ፣ እኔ እያለ በነቢያት በክርስቶስ፣ በሐዋርያት፣ እግዚአብሔር ሲያናግር ኑሯል፡፡  
  1.  (ዮሐ. 1፡1-3) በመጀመሪያ ቃል ነበረ፤ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ፡፡ ይህ በመጀመሪያ በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ፡፡ ሁሉም በእሱ ሆነ፡፡ ከሆነውም አንዳች ስንኳ ያለ እርሱ የሆነ የለም። ከዚህ ላይ ከመጀመሪያ ጀምሮ ከእግዚአብሔር አብ ጋራ ሌላ እግዚአብሔር ወልድ እንዳለ እና ያለእሱም ምንም  እንዳልሆነ ይናገራል፤ በአካል የተለያዩ በመለኮት ግን አንድ የሆኑ፤ ሁለት አካላት፤ አንድ እግዚአብሔር እንድ እግዚአብሔር እንዳለ  ወንጌላዊው ቁልጭ አድርጎ ገልጧል፤ ከዚህ ላይ የተጠቀሱት ሁለቱ አካላት አብና ወልድ ናቸው፣ ዝቅ ስንል ደግሞ ሦስት አካላት መሆናቸውን እናያለን፡፡ 
  2.    (ማቴ.3፡16-17) ኢየሱስም ከተጠመቀ በኋላ ወዲያው ከውኋ ወጣ፤ እነሆም ሰማያት ተከፈቱ የእግዚአብሔርም መንፈስ እንደ ርግብ ወርዶ ከእሱ ላይ ሲቀመጥ አየ፡፡ እነሆም ድምፅ ከሰማይት ወጥቶ በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው አለ፡፡ በዚህም በአምሰላ ርግብ  የወረደው እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ፤ የምወደው ልጄ ያለ እግዚአብሔር አብ ፤ ተጠማቂው ሰው የሆነው እግዚአብሔር ወልድ በትስብእቱ ዐማኑኤል፣ ኢየሱስ ክርስቶስ የተባለው፣በኋላ የቤተክርስቲያ ሊቃውንት ሥላሴ ብለው የሰየሟቸው አካላት፣ አብ ወልድ ወመንፈስ ቅዱስ መሆናቸውን ቁልጭ አድርጎ ያሳያል፡፡(ማር.1፡911፤ ሉቃ.3፡21-22) 
  3.   ይኽው ታሪክ በድብረ ታቦርም ተደግሟል፣ ያውም ከትእዛዝ ጋራ፣ (ማቴ.17፡1-6፤ማር.9፡2-13 ሉቃ.9.28-36)"እነሆም ከደመናው በእርሱ ደስ የሚለኝ ልጄ ይህ ነው እርሱን ስሙት፡፡"፥ 
  4.  (ዮሐ.11፡4) ኢየሱስም ሰምቶ፣ ይህ ሕመም የእግዚአብሔር ልጅ በእርሱ ይከብር ዘንድ ስለ እግዚአብሔር ክብር ነው እንጂ ለሞት አይደለም አለ፡፡ 
  5.    (ዮሐ.11፡-፡27) አዎ!ጌታ ሆይ አንተ ወደ ዓለም የሚመጣው ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆንህ እኔ አምናለሁ አለችው፡፡ በዚህ ጊዜ ቁርአንና እስላሞች እንደሚሉት አምላክ ባይሆን ኑሮ፣ አይደለሁም  ተሳስተሸል፣ እኔ አምላክ አይደለሁም ይላት ነበር፡፡ 

Wednesday, June 6, 2012

በደብረ ይድራስ ቅ/ጊዮርጊስ ተቃዋሚዎችን ለመበተን የተሰማራው ፖሊስ አስለቃሽ ጢስ ይዞ ቤተ መቅደስ ገባ

  • በአስለቃሽ ጢሱ ጸሎተ ቅዳሴው ታጉሏል፤ ሕፃናት፣ ምእመናንና አገልጋዮች ታፍነዋል:: 
  • ለውዝግቡ መፍትሔ ያፈላልጋል የተባለ ጥምር ኮሚቴ ተቋቁሟል:: 
  • ከ70 - 80 የሚደርሱ የደብሩ ሠራተኞችና ምእመናን እንደታሰሩ ናቸው::
  • ከንቲባ ኩማ ደመቅሳ ሊቀ ጳጳሱን በስልክ አነጋግረዋል::

 በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ በሚገኘው ደብረ ይድራስ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ከይዞታ ማስከበር ጋራ በተያያዘ ትናንት፣ ግንቦት 27 ቀን 2004 ዓ.ም ጠዋት በአጥቢያው ምእመናን መካከል ግጭት ተቀስቅሷል፤ በግጭቱ የአንድ ፖሊስ ሕይወት አልፏል፤ ስድስት ፖሊሶችና በርካታ ምእመናንም ተጎድተዋል፤ ብዙዎቹን የደብሩ ሰበካ ጉባኤ አባላትንና ሌሎች ሠራተኞችን ጨምሮ በቁጥር ከ70 - 80 የሚሆኑ የአጥቢያው ወጣት እና አዛውንት ምእመናን ከየመንደሩ በፌዴራል ፖሊስ አባላት እየተሰበሰቡ መታሰራቸው ነው የተነገረው፡፡

Wednesday, May 23, 2012

ቅዱስ ሲኖዶስ በተሐድሶ ኑፋቄ አራማጅ ድርጅቶች ላይ የቀረበውን ጥናታዊ መግለጫ እና የውሳኔ ሐሳብ አጸደቀ፤ ማ/ቅዱሳንም ከሰ/ት/ቤቶች መምሪያ ሥር እንዲወጣና ራሱን እንዲችል ወሰነ

የቅዱስ ሲኖዶስ ዐሥርኛ ቀን የቀትር በፊት ውሎ

  • በፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ አራማጅ ግለሰቦች ላይ የቀረበውን ጥናታዊ መግለጫና የውሳኔ ሐሳብ ደግሞ ከሰዓት በኋላ በመነጋገር እንደሚያጸድቀው ይጠበቃል:: 
  • ማኅበረ ቅዱሳን በአወቃቀሩ ከሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሥር ወጥቶ ለዋና ሥራ አስኪያጁ ተጠሪ እንዲኾን ቅዱስ ሲኖዶሱ ወስኗል
 የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በዛሬው ዐሥርኛ ቀን የቀትር በፊት ውሎው በስምንት የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ እንቅስቃሴ አራማጅ ድርጅቶች ላይ የብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት እና የሊቃውንት ጉባኤ አባላት ጥምር ኮሚቴ ያቀረበውን ጥናታዊ መግለጫ እና የውሳኔ ሐሳብ መርምሮ አጽድቋል፡፡

Friday, May 18, 2012

በብዙ ጫና ውስጥ ያለው ማ/ቅዱሳን መንግሥት በዋልድባ አካባቢ ስለሚገነባቸው ፕሮጄክቶች ሪፖርቱን አቀረበ

 ማ/ቅዱሳን መንግሥት በዋልድባ አካባቢው ሊሠራው ስላቀደው ግዙፍ ፕሮጄክት “አጠናሁት” ያለውን ሪፖርት አቀረበ፤ ከመንግሥት ጋር መነጋገሩንም ገለጸ። ዛሬ ይፋ የተደገው የማኅበሩ ሪፖርት የቤተ ክህነቱ አዳዲስ ተሿሚዎች ማኅበሩን በዋልድባ ጉዳይ በከሰሱ ማግስት የቀረበ ሲሆን ለእነርሱ ክስ የተሰጠ አፋጣኝ ምላሽ ይሁን አይሁን ወደፊት የሚታይ ይሆናል።
አዲስ የተሾሙት የሰንበት ት/ቤቶች ማ/መምሪያ ኃላፊ መምህር ዕንቁ ባሕርይ ተከስተ “በዋልድባ አካባቢ መንግሥት ሊሠራ ያቀደውን ግዙፍ የስኳር ፋብሪካን በማስመልከት በዋልድባ ይዞታ ላይ ያደረሰው ተጽእኖ መኖር አለመኖሩን የሚያጣራ ኮሚቴ ተቋቁሞ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ሁሉ ተፈላጊውን የማጣራት ሥራ አከናውኖ” ከተመለሰ በኋላ “ጋዜጣዊ መግለጫ መሰጠቱና … የማኅበረ ቅዱሳን ጋዜጠኞች መከታተላቸው መሣተፋቸውና የሚፈልጉትን ጥያቄ በይፋ አቅርበው ምላሽ መሰጠቱ”ን ጠቅሰው “ማንኛውም ጋዜጠኛ በተለይም ደግሞ የቤተ ክርስቲያኒቱ ልሣን የሆነው የማኅበሩ ጋዜጣና መጽሔት መረጃ ከወሰደ በኋላ መግለጫውን አለማውጣቱ አግባብነት የሌለው ከመሆኑም በላይ የሚዲያ ሥነ ምግባርንም ያልተከተለ ስለሆነ” ጽሑፉ ያልወጣበትን ምክንያት ማኅበሩ በጽሑፍ ይገልጽ ዘንድ ከሕዝብ ግንኙነት መምሪያ መታዘዛቸውን እንዳብራሩ መዘገባችን ይታወሳል።

የመምሪያው ደብዳቤ “ጋዜጣዊ መግለጫውን በሚዲያ ለማውጣት ተስማምታችሁ ሪፖርት እንድታደርጉ ከወሰናችሁ በኋላ ዘገባው የቀረበት ምክንያት በጽሑፍ ለማደራጃ መምሪያው” እንዲመለስ እንደሚጠብቅ በመግለጽ “ለፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር፣ ለብሔራዊ ደኅንነት አገልግሎትና ለፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን” ግልባጭ ተደርጓል። ደጀ ሰላምም “የቅ/ሲኖዶስ ጽ/ቤት፣ የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽ/ቤት፣ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት፣ የሕዝብ ግንኙነት መምሪያ እና ሕግ አገልግሎት መምሪያ የቤተ ክርስቲያናችን አካላት ስለሆነ በቀጥታም ባይሆን ጉዳዩ ሊያገባቸው ይችላል። ከላይ ስማቸው የተዘረዘሩት የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች በምን አግባብ ነው ስለ አንድ ማኅበር፣ ያውም በአንድ መምሪያ ሥር ስላለ አካል ግልባጭ የሚደረግላቸው? መንግስታዊ መሥሪያ ቤቶቹ ከሚዲያ ጋር የተገናኙ እንኳን ቢሆኑ በግድምድሞሽ “ግንኙነት አላቸው” ይባል ይሆናል። ፌዴራል ጉዳዮች፣ ደኅንነት፣ ፖሊስ … መጠቀሳቸው ለምን ያስፈልጋል? እሰሩልን፣ ግደሉልን፣ ቀፍዱድልን ለማለት ካልሆነ” ማለቷ ይታወሳል።

ቅ/ ሲኖዶስ በፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ አራማጅ ማኅበራትና ግለሰቦች ላይ የተዘጋጀውን ሪፖርት አዳመጠ

  • ኮሚቴው ፍጹም ውግዘት የሚገባቸውን የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ እንቅስቃሴ አራማጅ ማኅበራትና ግለሰቦች ለይቷል - ማኅበረ ሰላማ፣ ማኅበረ በኵር፣ የምሥራች አገልግሎት፣ አንቀጸ ብርሃን፣ የቅድስት ልደታ ለማርያም መንፈሳዊ ማኅበር፣ የኢትዮጵያ መንፈሳዊ ተሐድሶ ኅብረት፣ አሸናፊ መኰንን፣ አግዛቸው ተፈራ፣ ጽጌ ስጦታው እና ግርማ በቀለ ይገኙባቸዋል።
  • “ሃይማኖቴ እንደ አባቶቼ ነው” ያሉት የአባ ሰረቀ እና “የቅን ልቦና የመንፈሳዊና የፈውስ አገልግሎትን ያቋቋምኹት ልጆቼን የማበላቸው ስለተቸገርኹ ነው” ያሉት የ‹ሊቀ ካህናት› ጌታቸው ዶኒ ጉዳይ ያለውሳኔ ሐሳብ ለምልአተ ጉባኤው ውሳኔ ቀርቧል።
  • አባ ጳውሎስ ከጥንተ አብሶ ጋራ በተያያዘ ስለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ንጽሕና እንዲመሰክሩ ሊጠየቁ ይችላሉ።
  • ሊቃውንት ጉባኤው ተደጋጋሚ ጥሪ አድርጎለት ያልቀረበው በጋሻው ደሳለኝ ዛሬ ጠዋት የሊቃውንት ጉባኤውን ሰብሳቢ በእጅጋየሁ በየነ አማላጅነት ሲለማመጥ ታይቷል፤ ሊቃውንት ጉባኤው “በአንድ ወቅት በራስ ቅል ኮረብታ ላይ ኢየሱስና ዲያቢሎስ ቁማር ተጫወቱ . . . ዲያቢሎስም በጨበጣ ገባ” የሚለውና ሌሎቹም ጥንቃቄ የጎደላቸው ንግግሮቹ ፍጹም ውግዘት የሚገባቸው እንደኾኑ አመልክቷል።
  • የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን አመራርና መዋቅር ይሻሻላል፤ በጠቅላላ ጉባኤና በቦርድ ይመራል፤ የኮሚሽኑ ሊቀ ጳጳስ የኮሚሽኑ ኮሚሽነር እንደሚኾኑ ተጠቁሟል።
  • የማኅበራት መመሪያ ረቂቅ ለውይይት ቀርቧል፤ አሁን ባሉበት አኳኋን ከቀጠሉ “ሌላ ሲኖዶስ ይኾናሉ፤ የፖሊቲካ ዓላማ ማስፈጸሚያ ይኾናሉ፤ በቀኝ ዘመምና ግራ ዘመም አቋም ቤተ ክርስቲያኒቷን ይውጣሉ/ይከፍላሉ” የሚል ስጋት የቀረበባቸው ማኅበራት ንብረት በአጥቢያ አብያተ ክርስቲያን መዋቅር ውስጥ ተጠቃልሎ እንዲተዳደር ሐሳብ ቀርቧል፤ የመመሪያውን ረቂቅ በጥንቃቄ የተመለከቱት የምልአተ ጉባኤው አባላት ጉዳዩ በይደር እንዲታይ አድርገዋል።

 የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በግንቦት 8 ቀን 2004 ዓ.ም ስድስተኛ ቀን ውሎው በፕሮቴስታንት ድርጅቶች ከፍተኛ ድጋፍ እየተደረገላቸው የቤተ ክርስቲያናችንን ትምህርተ ሃይማኖት ለማፋለስ፣ ሥርዐተ እምነቷን ለመለወጥ፣ አገልጋዩንና ምእመኑን ለመከፋፈል በቡድንና በድርጅት ኾነው በመንቀሳቀስ ላይ ስለሚገኙት የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ አራማጅ ማኅበራትና ግለሰቦች የተዘጋጀውን ሪፖርት አዳምጧል፡፡

ቅዱስ ሲኖዶሱ በአጀንዳ ተ.ቁ (13) ላይ ስለ ሃይማኖት ሕጸጽ በተመለከተው ርእሰ ጉዳይ በጥቅምቱ ቅዱስ ሲኖዶስ መደበኛ ስብሰባ ከሊቃውንት ጉባኤ ጋራ በመኾን የቀረቡ ማስረጃዎችን መርምረው የውሳኔ ሐሳብ የሚያቀርቡ ሰባት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በአባልነት የሚገኙበት ኮሚቴ ሠይሞ ነበር፡፡

በወቅቱ የኮሚቴው አባላት እንዲኾኑ ተመርጠው የነበሩት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፡- ብፁዕ አቡነ ናትናኤል፣ ብፁዕ አቡነ ገሪማ፣ ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ፣ ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ፣ ብፁዕ አቡነ እንድርያስና ብፁዕ አቡነ ያሬድ ነበሩ፡፡ ጥቅምት 20 ቀን 2004 ዓ.ም ከተሠየመው ከእኒህ የኮሚቴው አባላት መካከል ሦስቱ (አቡነ ናትናኤል፣ አቡነ ቄርሎስ እና አቡነ እንድርያስ) በተለያየ ምክንያት መቀጠል ስላልቻሉ ቋሚ ሲኖዶሱ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስን፣ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስንና ብፁዕ አቡነ ኤጲፋንዮስን ተክቷል፡፡

ኮሚቴው ከሊቃውንት ጉባኤው የቀረበለትና መርምሮ በትናንትናው ዕለት ከቀትር በኋላ በጸሐፊው በኩል ለቅዱስ ሲኖዶስ በንባብ ያሰማው ሪፖርት ባለ60 ገጽ ሲኾን በዛሬው ዕለት ምልአተ ጉባኤው በሪፖርቱ ላይ በመወያየት የውሳኔ ሐሳቡን ያጸድቃል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ሪፖርቱ በፕሮቴስንታንት ድርጅቶች ከፍተኛ ድጋፍ እየተደረገላቸው ኦርቶዶክሳውያን መስለው በሁሉም የቤተ ክርስቲያን እንቅስቃሴዎች በመሳተፍ እና የአስተዳደር መዋቅሮች ውስጥ በመሰግሰግ ፕሮቴስታንታዊ አጀንዳቸውን ለማስፈጸም ከሚንቀሳቀሱት ማኅበራት መካከል በስምንቱ ላይ ያተኮሩ የኅትመት ውጤቶችን፣ የድምፅ እና ምስል ማስረጃዎችን መርምሯል፡፡

የፕሮቴስታንት እምነት ተቋማት ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጋራ ያላቸውን የመሠረተ እምነት /ዶግማ/ ልዩነት /ድንበር/ አጥፍተው ቤተ ክርስቲያናችንን በቁጥጥር ሥር አውለው ባለችበት ፕሮቴስታንታዊ ማድረግ ወይም ቤተ ክርስቲያናችንን  የጦርነት ቀጣና በማድረግ እንደ ሕንድ ቤተ ክርስቲያን ለሁለት መክፈል ዓላማ ያላቸው ማኅበራቱ በአሁኑ ሰዓት በሚያወጧቸው መጻሕፍትና መጽሔቶች እንዲሁም በራሪ ወረቀቶች የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ በግልጽ ይቃወማሉ፤ አገልጋዩና ምእመኑ በማይመች አካሄድ እንዲጠመድ እና በዘረኝነት እንዲከፋፈል ጭምር ይንቀሳቀሳሉ፡፡ ይህም በማስረጃ ተደግፎ የቀረበ በመኾኑ ፍጹም መወገዝ ያለባቸው ማኅበራት ተለይተው ቀርበዋል፡፡

ከእኒህም ውስጥ ኮሚቴው ፍጹም ውግዘት እንዲተላለፍባቸው የውሳኔ ሐሳብ ከቀረበባቸው የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ አራማጅ ማኅበራት መካከል፡-
1.   ማኅበረ ሰላማ - በክልል ትግራይ ፍትሕ ቢሮ ተመዝግቦ ፈቃድ ባወጣበት ስሙ ማኅበረ ሰላማ ምትሕግጋዝ ማኅበር (Abune Selama Self Help Association) እየተባለ የሚጠራና ዋና ጽ/ቤቱ መቐለ የሚገኝ ነው፡፡ ባወጣው ፈቃድ መሠረት በልማት ሥራ ላይ መሳተፍ ሲገባው ከሕገ ወጥ ባሕታውያንና ሌሎች የተሐድሶ ማኅበራት ጋራ በመቀናጀት ‹‹በገዳማት ላይ ጥናት ማድረግ›› በሚል ሰበብ በቅርሶች ላይ ከፍተኛ ዘመቻ በማካሄድ ማንነትን ለማጥፋትና በአቋራጭ ለመክበር ይንቀሳቀሳል፤ ዘረኝነትን ያስፋፋል፡፡ የአሲራ መቲራው ገዳም አበምኔት ነኝ ባዩ አባ ገብረ መድኅን ገብረ ጊዮርጊስ ከማኅበሩ መሪዎች ጋራ በድብቅ በመገናኘት ዕቅዱን ለማስፈጸም ይንቀሳቀሳል፡፡
2.   ማኅበረ በኵር - በ1983 ዓ.ም የተመሠረተ ሲኾን መሥራቹ በ1953 ዓ.ም ከቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የተባረረው መሠረት ስብሐት ለአብ ነው፡፡ ከምሥረታው ጀምሮ ሙሉ በሙሉ በፕሮቴስታንቶች ድጋፍ ላይ የተመሠረተ ነው፡፡ ሌሎች የተሐድሶ ኑፋቄ ማኅበራት ‹‹አርኣያችን ነው›› ይሉታል፡፡ ጮራየተሰኘ መጽሔት ያሳትማል፡፡ መጽሔቱን በሕገ ወጥ መንገድ ለብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ለሰንበት ት/ቤቶችና ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ግቢ ግባኤያት ይልካሉ፡፡ በአሁኑ ወቅት  አግዛቸው ተፈራ የተባለው በዋና አዘጋጅነት በሚሠራበት መጽሔት የጸሎት መጻሕፍትን ይቃወማሉ፤ አባቶችን ይዘልፋሉ፤ አዋልድ መጻሕፍትን አይቀበሉም፤ ‹‹ቅዱሳት ሥዕላት አያስፈልጉም›› ይላሉ፤ ‹‹ኢየሱስ ክርስቶስ አሁንም አማላጅ ነው››፤ ሥልጣነ ክህነትን አይቀበሉም፤ የእምነት ልዩነት ድንበርን ያፈርሳሉ፤ ‹‹ቅዱስ ቍርባን መታሰቢያ ነው፤ ውላጤ ኅብስት የለም›› ይላሉ፤ ምስጢረ ሜሮንን ይቃወማሉ፤ ‹‹ሥጋ በተዋሕዶ የባሕርይ አምላክ አልኾነም›› ይላሉ፡፡
3.   የምሥራች አገልግሎት - በ1990 ዓ.ም የተመሠረተና አሸናፊ ሲሳይ በተባለ ግለሰብ የሚመራ ሲኾን ‹‹ቤተ ክርስቲያን የውጊያ ቀጣና ናት›› በማለት ለእንቅስቃሴው የሚረዱ 34,000 ‹‹እርሾዎችን›› በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ለመሰግሰግ ከፍተኛ የገንዘብና የማቴሪያል ድጋፍ የሚደረግለት፣ እያንዳንዳቸው ከ100 - 160 አባላት ባሉት ኅቡእ ቡድን (Cell based) የሚንቀሳቀስ አካል ነው፡፡ ‹‹ፕሮቴስታንት እና ኦርቶዶክሳውያን በመሠረተ እምነት አንድ ናቸው›› ከሣቴ ብርሃን ከተባለው ድርጅት ጋራ አንድ ዐይነት ዓላማ ያራምዳል፤ የክርስቶስን አምላክነት በአግባቡ አያምንም፤ ምንኵስናን ይቃወማል፤ አዋልድ መጻሕፍትን አይቀበልም፡፡
4.   አንቀጸ ብርሃን - ከሰበታ መካነ ሰላም ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ፍሬ ሃይማኖት ሰንበት ት/ቤት ተለይቶ የወጣው አሸናፊ መኰንን የሚያሳትማቸውን የኑፋቄ መጻሕፍት ያስተዋውቃል፡፡ በሌላ ስያሜው ራሱን ‹‹ማኅበረ መንፈስ ቅዱስ›› እያለ ይጠራል፡፡ ‹‹የኢ////ያን እምነትና ሥርዐት የጠበቀ መንፈሳዊ ጽሑፍ›› በሚል በኅቡእ በሚያሰራጫቸው ጽሑፎቹ ምሥጢረ ሥላሴን አፋልሶ ያስተምራል፤ ምስጢረ ሥጋዌን በማፋለስ ቅብዐትን ይሰብካል፤ በካህን ፊት የሚደረግ ኑዛዜን ይቃወማል፡፡
5.   የቅድስት ልደታ ለማርያም መንፈሳዊ ማኅበር - በኑፋቄያቸው ከማኅደረ ስብሐት ልደታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን ተክለ ሳዊሮስ ሰንበት ት/ቤት የተሰናበቱ ተወግዞ የተባረረው የሃይማኖተ አበው ማኅበር ሰለባዎች ነው፡፡ አቶ መስፍን በተባለ ግለሰብ ይመራል፡፡ ኦርቶዶክሳውያን ወደ ፕሮቴስታንትነት መቀየራቸውን ሳያውቁት ሃይማኖታቸውን የሚያስክዱ የርቀት ትምህርቶችን ይሰጣል፤ ኅትመቶችን ያሰራጫል፤ ቤተ ክርስቲያንን በግልጽ ይዘልፋል፤ የሥጋ ወደሙን አማናዊነት አያምንም፡፡
6.   የእውነት ቃል አገልግሎት - ድርጅቱ ይህን ስያሜ ከመያዙ በፊት በመጀመሪያ BGNLJ (Brothers Gathered Unto Lord Jesus) በኋላም (Bible Truth Ministry) እየተባለ ይጠራ ነበር፡፡ በአሁኑ ጊዜ የድርጅቱ መሪ በቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ ደቀ መዛሙርትና ማኅበረሰብ ብርታት የተባረረው ግርማ በቀለ ነው፡፡ ሌላው ተጠቃሽ ግለሰብ ሥዩም ያሚ የሚባለው ነው፡፡ ድርጅቱ ከእንግሊዝኛ በሚተረጉማቸው መጻሕፍት የቤተ ክርስቲያንን መጻሕፍት ክፉኛ ያብጠለጥላል፤ በየክልሉ በከፈታቸው ቅርንጫፍ ማከፋፈያዎች ጽሑፎችን በነጻ በማደል፣ ሥልጠናዎችን በመስጠት፣ ታሪክን በማዛባትና በአዋልድ መጻሕፍት ላይ የማይገባ ትችት በመሰንዘር አገልጋዮችን ያደናግራል፡፡

Thursday, May 17, 2012

ማ/ቅዱሳን መንግሥት በዋልድባ አካባቢ ስለሚገነባው የስኳር ፕሮጄክት “መልካምነት” ባለመዘገቡ ተጠየቀ፤ መልስ እንዲሰጥ ይጠበቃል


አስከትሎም “ስለሆነም ማንኛውም ጋዜጠኛ በተለይም ደግሞ የቤተ ክርስቲያኒቱ ልሣን የሆነው የማኅበሩ ጋዜጣና መጽሔት መረጃ ከወሰደ በኋላ መግለጫውን አለማውጣቱ አግባብነት የሌለው ከመሆኑም በላይ የሚዲያ ሥነ ምግባርንም ያልተከተለ ስለሆነ” ጽሑፉ ያልወጣበትን ምክንያት ማኅበሩ በጽሑፍ ይገልጽ ዘንድ ከሕዝብ ግንኙነት መምሪያ መታዘዙን ያብራራል።

የመምሪያው ደብዳቤ አክሎም “ጋዜጣዊ መግለጫውን በሚዲያ ለማውጣት ተስማምታችሁ ሪፖርት እንድታደርጉ ከወሰናችሁ በኋላ ዘገባው የቀረበት ምክንያት በጽሑፍ ለማደራጃ መምሪያው” እንዲመለስ እንደሚጠብቅ ይገልጻል። ደብዳቤው በአድራሻ ለማኅበሩ ከተላከ በኋላ ደግሞ ለቤተ ክህነቱ የተለያዩ አካላትና በመንግሥትም በኩል “ለፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር፣ ለብሔራዊ ደኅንነት አገልግሎትና ለፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን” ግልባጭ ተደርጓል።

የቅ/ሲኖዶስ ጽ/ቤት፣ የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽ/ቤት. የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት፣ የሕዝብ ግንኙነት መምሪያ እና ሕግ አገልግሎት መምሪያ የቤተ ክርስቲያናችን አካላት ስለሆነ በቀጥታም ባይሆን ጉዳዩ ሊያገባቸው ይችላል። ከላይ ስማቸው የተዘረዘሩት የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች በምን አግባብ ነው ስለ አንድ ማኅበር፣ ያውም በአንድ መምሪያ ሥር ስላለ አካል ግልባጭ የሚደረግላቸው? መንግስታዊ መሥሪያ ቤቶቹ ከሚዲያ ጋር የተገናኙ እንኳን ቢሆኑ በግድምድሞሽ “ግንኙነት አላቸው” ይባል ይሆናል። ፌዴራል ጉዳዮች፣ ደኅንነት፣ ፖሊስ … መጠቀሳቸው ለምን ያስፈልጋል? እሰሩልን፣ ግደሉልን፣ ቀፍዱድልን ለማለት ካልሆነ።

Monday, May 14, 2012

አቡነ ጳውሎስ ከፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ መናፍቃን ጋራ ማበራቸውን የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ገለጹ

 (ምንጭ ደጀ ሰላም፤ ግንቦት 5/2004 ዓ.ም፤ May 13/ 2012)፦



  • ቅዱስ ሲኖዶስ በቀጣይ ለሚኖረው አመራር የመላው ካህናትና ምእመናን ጸሎትና ሁለንተናዊ ድጋፍ እንዲደረግለት ተጠይቋል 
  • በአባ ጳውሎስ፣ አባ ፋኑኤልና ኀይለ ጊዮርጊስ ጥላሁን ምክርና ኮሚሽን አድራጊነት የተጻፈው የዜና ቤተ ክርስቲያን ጋዜጣ ርእሰ አንቀጽ እና ዘገባ በፈጠረው ቁጣ ሳቢያ የቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባ ተቋረጠ 
  • ጋዜጣው በስብሰባ መካከል መሰራጨቱና ባተኮረበት ይዘት ብፁዓን አባቶችን ለማሸማቀቅ ተብሎ መዘጋጀቱን የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ተናግረዋል 
  • የጋዜጣው ርእሰ አንቀጽና ዘገባዎች አባ ጳውሎስ በስብሰባው እንዲያዙላቸው የሚፈልጓቸውን አጀንዳዎች ከአባ ጳውሎስ “የፓትርያርክነት ዐምባገነንነት” ፍላጎት አንጻር የማብራራት ግብዝነት የሚታይበት ነው
  • አባ ጳውሎስን ከፓትርያርክነት ማዕርጋቸው በሚያወርዷቸው የቃለ መሐላ ጥሰትና የታማኝነት መታጣት ጉዳዮች ዙሪያ ጠንካራ ውይይት ተጀምሯል
  • የአባ ጳውሎስ ግብረ በላዎች ትንት ማምሻውንና ዛሬ ቀን በአባቶች ማረፊያ ቤት እየተዘዋወሩ በማስፈራራት ጽናታቸውንና አንድነታቸውን ለማላላት እየሞከሩ ነው፤ እጅጋየሁ በየነ፣ ኀይለ ጊዮርጊስ ጥላሁንና ለጊዜው ስማቸው ያልተጠቀሱ ግለሰቦች ይገኙባቸዋል
  • መደበኛ ስብሰባው ነገ ሰኞ ይቀጥላል
  ግንቦት 4 ቀን 2004 ዓ.ም ከቀትር በፊት በነበረው የቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባ ርእሰ መንበሩ አባ ጳውሎስ በምልአተ ጉባኤው ስምምነት የተደረሰባቸውን አጀንዳዎች ባለመቀበል ኾነ ብለው በያዙት ግትርነት የተነሣ ብዙኀኑ አባላት ከቀትር በኋላ ሌላ ሰብሳቢ መርጠው ውይይታቸውን ለመቀጠል ወስነው ነበር የተነሡት፡፡
በዚህ መሠረት የቅዱስ ሲኖዶሱ አባላት ከቀትር በኋላ ስብሰባውን ለመቀጠል ወደ አዳራሹ ሲገቡ የዜና ቤተ ክርስቲያን ጋዜጣ በየመቀመጫቸው አንጻር ተቀምጦ ያገኛሉ፤ ፓትርያርኩም በኮሚቴው የተዘጋጁትን አጀንዳዎች እንደሚቀበሉ መስለው ተላስልሰው በመቅረባቸው ምልአተ ጉባኤው በእርሳቸው ርእሰ መንበርነት እየተመራ በተ.ቁ (2) ላይ የተመለከተውን የቅዱስ ሲኖዶሱን ዋና ጸሐፊ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤልን ሪፖርት አዳመጠ፤ እግረ መንገዳቸውንም ጋዜጣውን እንደ ዋዛ መመልከታቸውን አላቆሙም ነበር፡፡
ሪፖርቱ በንባብ ተሰምቶ ከተጠናቀቀ በኋላ ውይይት ከመጀመሩ በፊት ለሻሂ ዕረፍት የተነሡት አባቶች ግን ጋዜጣው በያዘው ‹ቁም ነገር› ላይ መመካከር ያዙ፤ ምክክሩም አቡነ ጳውሎስ ከስብሰባው ቀደም ብለው ከዋሽንግተን ወደ አገር ቤት ከመጡት አባ ፋኑኤል እና ኀይለ ጊዮርጊስ ጥላሁን ጋራ በማበር የጋዜጣውን አዘጋጆች እና ጋዜጣው በሚዘጋጅበት መምሪያ ውስጥ በሓላፊነት የሚገኙ ሌሎች ግለሰቦችን በቅጥረኝነት በመጠቀም የሠሩት መኾኑን ይደርሱበታል፡፡
ከሻሂ ዕረፍት መልስ ጋዜጣው ምን እንደጻፈ፣ ስለምን እንደጻፈ ሊያውቅና ሲቆጣጠርም ይገባ የነበረው  የስብከተ ወንጌል እና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ ስለ ጋዜጣው ዝግጅት ምንም እንደማያውቁና ሌሎች አጀንዳዎች ወደ ኋላ ቀርተው ምልአተ ጉባኤው በዚሁ ጉዳይ እንዲነጋገር ይጠይቃሉ፡፡ ከዚህ በኋላ በቤቱ የነበረው ድባብ በፓትርያርኩ እና በአባ ፋኑኤል ላይ ባነጣጠረ የተግሣጽ መአት የተሞላ ነበር፡፡ አባ ጳውሎስም ይኹኑ አባ ፋኑኤል የሠሩትን ያውቃሉና አንገታቸውን አቀርቅረው ተግሣጻቸውን ከመቀበል ውጭ ትንፍሽ ያሉት ነገር አልነበረም፡፡
በተግሣጹ አባ ጳውሎስ ከተሐድሶ መናፍቃን ጋራ በግልጽ በማበር አባቶች በወቅታዊ ጉዳዮች በተቀረጹት አጀንዳዎች ዙሪያ ያላቸውን አንድነት እና የዓላማ ጽናት በመሸርሸር ለማሸማቀቅ (በግብር የሚመስሏቸው የመፍቀሬ ፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ብሎጎች እንደሚያደርጉት) አስበው እንዲፈጸም በማዘዝ እጃቸው እንዳለበት ተነግሯቸዋል፤ አባ ፋኑኤልም “መወገዝ ያለብኽ ሕገ ወጡ አንተ ነኽ፤ በሌላው ሊቀ ጳጳስ ሀገረ ስብከት ገብተኽ ክህነት የምትሰጥ፤ አንተ ብሎ ክህነት ያዥ¡” በሚሉና ሌሎችም ኀይለ ቃላት የድርሻቸውን አግኝተዋል፡፡
በ56ኛ ዓመት ቁጥር 126፣ ሚያዝያ ግንቦት 2004 ዓ.ም ታትሞ በወጣው ዜና ቤተ ክርስቲያን ጋዜጣ ላይ ‹‹የአባቶች ገበና በሕገ ቤተ ክርስቲያን ሲጋለጥ›› በሚል ርእስ ስለ ሰፈረው ርእሰ አንቀጽ፣ ‹‹ቤተ ክርስቲያንንና መንጋዎቿን ከወቅታዊ አደጋ ለመታደግ ከግንቦቱ ቅዱስ ሲኖዶስ የሚጠበቅ የህልውና ውሳኔ›› በሚል ርእስ ስለተዘጋጀው ሐተታ አስተያየታቸውን የተጠየቁት ዋና አዘጋጁ መጋቤ ምስጢር ወልደ ሩፋኤል ፈታሒ ‹‹እኔ ማንንም አልፈራም፤ ጽሑፉ አያስጠይቀኝም እንጂ ብጠየቅበት አልፈራም፤ በይዘቱ አዲስ አይደለም፤ የተለያዩ ግለሰቦች በየራሳቸው አቀራረብ ሲጽፉት የቆዩት ነው፤ እኔ ለመጻፍ የሞከርኹት የቤተ ክርስቲያን ህልውና እየተነካ ነው ብዬ በማምንበት ስለ ጳጳሳት ንብረት ጉዳይ ነበር፤ አባ ጳውሎስ ግን በሲኖዶስ ስብሰባ ሕገ ቤተ ክርስቲያን ይሻሻል አሉ፤ እውነቱን ለመናገር  ጽሑፉ ከውጭ የመጣ እንጂ በዝግጅት ክፍሉ የተጻፈ አይደለም፤ በስሜ እየተነገደብኝ ነው፤›› ብለዋል፡፡
ዋና አዘጋጁ ጽሑፉ ከውጭ ተዘጋጅቶ እንደመጣ የተናገሩትን መነሻ በማድረግ አዘጋጁን አካል ለማወቅ በተደረገ ጥረት÷ ‹‹አባ ጳውሎስን ደግፋችኹ ከጻፋችኹ ማንም አይነካችኹ፤ ከተነካችኹም እኛ አለንላችኹ፤ ሁሉም ወንጀለኛ ነው›› በሚል የጥቅም ማበረታቻ የተቀበሉት የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ሕዝብ ግንኙነት መምሪያ ዋና ሓላፊ እስክንድር ገብረ ክርስቶስ፣ በስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ ዋና ሓላፊነት ባለው ሥልጣን ቀናዒ ኦርቶዶክሳውያንን ከመድረክ እያገለለና በየአህጉረ ስብከቱ በመዞር ከፕሮቴንታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ አራማጆችና አቀንቃኞች ጋራ ያለውን ግንኙነት እያጠናከረ የሚገኘው አእመረ አሸብር፣ እንደ ቀበሮዋ ዘለው ዘለው የሻቱትን ማዕርገ ጵጵስና ቢያጡት የተሾሙትን አባቶች በማሸማቀቅና አንገት በማስደፋት ለመሾም የቋመጡት አባ ሰረቀ፤ ለዚህም የገንዘብ ድጋፍ የሰጡት አባ ፋኑኤልና ዦቢራው ኀይለ ጊዮርጊስ ጥላሁን መኾናቸው እየተነገረ ነው፤ የአባ ጳውሎስ አይዟችኹ ባይነት (ቡራኬ) ሳይዘነጋ ማለት ነው፡፡ ይኹንና የዝግጅት ክፍሉም በጽሑፉ ላይ ማሻሻያ በማድረግና እንዲታተም በመፍቀድ፣ ምናልባትም የጥቅሙም ተካፋይ በመኾን መጠየቁ እንደማይቀር ግልጽ ነው፡፡